ወርቅነህ ገበየሁ (ዶ/ር) ከአዲሱ የአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን ሊቀመንበር ጋር ተወያዩ
አዲስ አበባ፣ መጋቢት 1፣ 2017 (ኤፍ ኤም ሲ) የምስራቅ አፍሪካ የልማት በይነ መንግስታት (ኢጋድ) ዋና ፀሐፊ ወርቅነህ ገበየሁ (ዶ/ር) ከአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን ሊቀመንበር መሐሙድ አሊ ዩሱፍ ጋር ተወያይተዋል።
በውይይታቸውም ወርቅነህ ገበየሁ (ዶ/ር) አዲሱ ሊቀመንበር የኢጋድ የሚኒስትሮች ም/ቤት ኃላፊ በነበሩበት ወቅት እና በተለያዩ ጊዜያት የቀጣናው ፈተናዎች እንዲፈቱ ያሳዩትን ቁርጠኝነትና ጠንካራ አመራር ሰጪነት አድንቀዋል።
የስልጣን ዘመናቸው ስኬታማ እንዲሆን መልካም ምኞታቸውን የገለጹት ዋና ጸሐፊው÷ኢጋድና የአፍሪካ ህብረት በቀጣናውና በአፍሪካ ሰላምን፣ ደህንነትንና ብልጽግናን ለማስፈን የጀመሩትን የጋራ ስራ አጠናክረው እንደሚቀጥሉ እምነታቸው መሆኑን አንስተዋል፡፡
ወርቅነህ ገበየሁ (ዶ/ር) በማህበራዊ ትስስር ገጻቸው ባሰፈሩት ጽሑፍ ÷መሐሙድ አሊ ዩሱፍ በአፍሪካ ቀጣይነት ያለው ትብብር፣ ዘላቂ ሰላም፣ መረጋጋት እና ብልጽግናን የሚያጠናክር ሥራ እንዲሰሩ መልካም ምኞታቸውን ገልጸዋል፡፡