Fana: At a Speed of Life!

ጾመ ፍልሰታን ስለሀገር ሰላም በመጸለይና ችግር ውስጥ የሚገኙ ወገኖችን በመርዳት ልናሳልፍ ይገባል – ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ

አዲስ አበባ፣ ሐምሌ 30፣ 2017 (ኤፍ ኤም ሲ) ጾመ ፍልሰታን ስለሀገር ሰላም በመጸለይ እና ችግር ውስጥ የሚገኙ ወገኖችን በመርዳት ልናሳልፍ ይገባል አሉ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ፓትርያርክ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ፡፡

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ የ2017 ዓ.ም የቅድስት ድንግል ማርያም ጾመ ፍልሰታን አስመልክተው የእንኳን አደረሳችሁ መልዕክት አስተላልፈዋል፡፡

በመልዕክታቸውም እኛ በየጊዜው ጾምን እንድንጾም ያስፈለገበት ዋናው ምክንያት ፈቃደ ሥጋችንን በመግራት ለእግዚአብሔር ታዛዦች እንድንሆን ነው ብለዋል፡፡

ጾም የኃጢኣት መግቻ መሳሪያ በመሆኑ ሰውነታችንን ለግብረ ኃጢኣት ከሚያጋግሉ ምግቦች አርቀን በሰከነ መንፈስ እግዚአብሔርን እያሰብን ኃጢኣታችንንም እያስታወስን በንስሓ ወደ እርሱ ለመቅረብና ለሱ ለመታዘዝ እንጾማለን ነው ያሉት፡፡

እግዚአብሔር ከመሥዋዕት ይልቅ መታዘዝን ይወዳልና በጾምና በጸሎት ለሱ ልንታዘዝ ይገባል፤እግዚአብሔር በቅድስት ድንግል ማርያም ማሕፀን ሊያድር የቻለው ‹‹እንዳልኸኝ ይሁንልኝ›› ብላ ታዛዥነትዋን በገለጸች ጊዜ ነው፤ እኛም እንዳልከን ይሁንልን እያልን እንደ እርሷ ታዛዥ መሆን አለብን ሲሉም ተናግረዋል፡፡

ዛሬ በዓለማችን ያለው መተረማመስ ለእግዚአብሔር ያለመታዘዝ ያመጣው ጣጣ እንደሆነ ማንም አይስተውም፤ መታዘዙ ቢኖር ኖሮ የሰው ልጅ ሰውን የሚያድን ብቻ እንጂ ሰውን የሚገድል መሳሪያ አያመርትም ነበር ብለዋል ብፁዕነታቸው በመልዕክታቸው፡፡

ከዚህ አንጻር ዛሬም ለሰው ልጆች ሁሉ የምናስተላልፈው መልዕክት ‹‹በፍቅር ከሆነ ትንሹም ለሁሉ ይበቃልና ያለውን በጋራ በመጠቀም በፍቅርና በሰላም እንኑር›› የሚል ነው ሲሉ አጽንኦት ሰጥተዋል፡፡

በጾመ ማርያም ሱባዔ ስለሀገር ሰላምና ስለሕዝብ ደኅንነት በመጸለይ፣ በልዩ ልዩ ምክንያት ችግር ውስጥ የሚገኙ ወገኖችን በመርዳት ልናሳልፍ ይገባል ሲሉ ማስገንዘባቸውንም ቤተክርስቲያኗ ለፋና ዲጂታል የላከችው መረጃ ያመላክታል፡፡

ፈጣን እና ወቅታዊ መረጃዎችን ለማግኘት፡-

YouTube www.youtube.com/@fanamediacorporation
Facebook www.facebook.com/fanabroadcasting
Telegram t.me/fanatelevision
Website www.fanamc.com
TikTok www.tiktok.com/@fana_television
WhatsApp www.whatsapp.com/channel/0029VbB0dRxG8l59MUkoWR29
Amharic Entertainment YouTube www.youtube.com/@fanaentertainment
Facebook www.facebook.com/wmccwaltamediaandcommunicationcorporate
TikTok www.tiktok.com/@fanamc_entertainment
Amharic Documentary YouTube www.youtube.com/@fanamcdocumentary በመወዳጀት ይከታተሉን፡፡
ዘወትር፦ ከእኛ ጋር ስለሆኑ እናመሰግናለን!

You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.