Fana: At a Speed of Life!

የፖለቲካ ሥርዓትን ለማዘመን በፉክክርና ትብብር መካከል ሚዛን መጠበቅ ያስፈልጋል – አቶ አደም ፋራህ

አዲስ አበባ፣ ጥቅምት 16፣ 2018 (ኤፍ ኤም ሲ) የፖለቲካ ሥርዓትን ለማዘመን በፉክክርና ትብብር መካከል ሚዛን መጠበቅ ያስፈልጋል አሉ የብልጽግና ፓርቲ ምክትል ፕሬዚዳንት አቶ አደም ፋራህ።

የአማራ ክልል መንግሥትና የፖለቲካ ፓርቲዎች የጋራ ምክር ቤት አባላት የምክክር መድረክ በባሕር ዳር ከተማ እየተካሄደ ነው።

በመድረኩ አቶ አደም ፋራህ፣ ርዕሰ መስተዳድር አቶ አረጋ ከበደ፣ የኢትዮጵያ የፖለቲካ ፓርቲዎች የጋራ ምክር ቤት ሰብሳቢ አቶ ሰሎሞን አየለ፣ የክልሉ የፖለቲካ ፓርቲዎች የጋራ ምክር ቤት ሰብሳቢ አቶ ተስፋሁን ዓለምነህ እንዲሁም ከተፎካካሪ ፓርቲዎች የተወከሉና ሌሎች ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎች ተገኝተዋል።

አቶ አደም ፋራህ በዚህ ወቅት እንዳሉት÷ የፖለቲካ ሥርዓትን ለማዘመን በፉክክርና ትብብር መካከል ሚዛን መጠበቅ ያስፈልጋል።

ጤናማና ውጤታማ ፉክክር ከጤናማ የፖለቲካ ምኅዳር የሚመነጭ በመሆኑ ፓርቲዎች ሕገ መንግሥቱ የሰጠውን ማዕቀፍ በመጠቀም መንቀሳቀስ እንደሚገባቸው አስገንዝበዋል።

ጤናማ ፉክክር እንዲኖር ለማስቻል የፖለቲካ ፓርቲዎች የራሳቸውን ሚና መወጣት እንዲችሉና የሕዝቡን ፍላጎት መሰረት ያደረጉ አጀንዳዎችን ይዘው እንዲሠሩ እንዲሁም ሕግና መርህን ማክበር እንደሚኖርባቸውም ነው የተናገሩት።

አቶ አረጋ ከበደ በበኩላቸው÷ የፖለቲካ ፓርቲዎች የጋራ ምክክር የዴሞክራሲ ልምምዳችን ሥር እንዲሰድና ጠንካራ የዴሞክራሲ ሥርዓት እንዲዳብር የሚያስችል ነው ብለዋል።

ለሰላም፣ ልማትና ሁለንተናዊ የሕዝብ ተጠቃሚነት ሁነኛ ሚና እየተጫወቱ ያሉ የፖለቲካ ፓርቲዎች እንዳሉ ሁሉ ዴሞክራሲን አደጋ ላይ የሚጥሉ አሰላለፎች የያዙና በኃይል መንግሥትን የመናድ ተግባርና ፍላጎት ያላቸውም መኖራቸውን ተናግረዋል።

ፓርቲዎች የፖለቲካ ስልጣንን በኃይል ለመያዝ የሚደረግን ፍላጎት በመግታት ዴሞክራሲን በሁለት እግሩ ለማቆም መሥራት ይገባልም ነው ያሉት።

ፓርቲዎች ሲመሰረቱና ፈቃድ ሲያገኙ የሀገሪቱን ሕግ አክብረው ሊሰሩ የገቡትን ቃል በማክበር ዴሞክራሲያዊ ትግላቸውን ማስቀጠልና ሕግና ሥርዓትን አክብረው መንቀሳቀስ እንደሚገባቸው አስገንዝበዋል።

የአማራ ክልል መንግሥት ከፖለቲካ ፓርቲዎች ጋር የምክክር መድረክ ማካሄዱ የሚበረታታና መልካም ተሞክሮ መሆኑን ያነሱት ደግሞ የኢትዮጵያ ፖለቲካ ፓርቲዎች የጋራ ምክር ቤት ሰብሳቢ አቶ ሰሎሞን አየለ ናቸው።

ፓርቲዎች ለዴሞክራሲ ሥርዓት ግንባታ ከሚያደርጉት አስተዋጽኦ ጎን ለጎን የክልሉን ሕዝብ የሰላም፣ ዴሞክራሲና ልማት ፍላጎት ለማሟላት የበኩላችንን አስተዋጽኦ ማድረግ ይገባናል ብለዋል።

በደሳለኝ ቢራራ

ፈጣን እና ወቅታዊ መረጃዎችን ለማግኘት፡-

YouTube www.youtube.com/@fanamediacorporation
Facebook www.facebook.com/fanabroadcasting
Telegram t.me/fanatelevision
Website www.fanamc.com
TikTok www.tiktok.com/@fana_television
WhatsApp www.whatsapp.com/channel/0029VbB0dRxG8l59MUkoWR29
Amharic Entertainment YouTube www.youtube.com/@fanaentertainment
Facebook www.facebook.com/wmccwaltamediaandcommunicationcorporate
TikTok www.tiktok.com/@fanamc_entertainment
Amharic Podcast YouTube www.youtube.com/@fanamcpodcast በመወዳጀት ይከታተሉን፡፡
ዘወትር፦ ከእኛ ጋር ስለሆኑ እናመሰግናለን!

You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.