የማርበርግ ቫይረስን ለመቆጣጠር የተቀናጀ ስራ እየተሰራ ነው – አቶ ጥላሁን ከበደ
አዲስ አበባ፣ ሕዳር 12፣ 2018 (ኤፍ ኤም ሲ) የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ጥላሁን ከበደ የማርበርግ ቫይረስን ለመከላከልና ለመቆጣጠር ከጤና ሚኒስቴር ጋር የተቀናጀ ስራ እየተሰራ ነው አሉ፡፡
ርዕሰ መስተዳድሩ እና የጤና ሚኒስትር ዶ/ር መቅደስ ዳባ በጂንካ ሆስፒታል ተገኝተው የማርበርግ ቫይረስ የመከላከልና የክትትል ስራዎች ምልከታ አድርገዋል፡፡
ከምልከታው በኋላ ርዕሰ መስተዳድሩ እንዳሉት፤ የበሽታውን ስርጭት ለመቆጣጠርና ተጨማሪ ጉዳት እንዳያስከትል ለመከላከል ፈጣን ምላሽ መስጫ ማዕከል ጂንካ ላይ ተቋቁሟል።
በዚህም የተቀናጀ የአስቸኳይ ጊዜ ምላሽ በመሰጠት ላይ እንደሆነ ተናግረዋል።
ጤና ሚኒስቴር ከክልሉ መንግሥት ጋር በቅርበት እየሰራ መሆኑን ገልጸው፤ ሚኒስቴሩ በሽታውን በምርመራ ለመለየት የሚያስችል ከፍተኛ የመመርመር አቅም ያለው ተንቀሳቃሽ ላቦራቶሪን ጨምሮ አስፈላጊ የቁሳቁስ ድጋፍ አድርጓል ብለዋል።
ርዕሰ መስተዳድሩ ህብረተሰቡ የበሽታውን መተላለፊያ መንገዶች በመገንዘብ አስፈላጊውን ጥንቃቄ እንዲያደርግ እና ተጋላጭነትን በመቀነስ ራሱን ከበሽታው እንዲከላከል ጥሪ አቅርበዋል።
የጤና ሚኒስትር ዶ/ር መቅደስ ዳባ በበኩላቸው በሽታው እንደተከሰተ ፈጣን ምላሽ ሰጪ ቡድኖች ቫይረሱ ወደ ተገኘባቸው አካባቢዎች ተንቀሳቅሰው የተቀናጀ የአስቸኳይ ጊዜ ምላሽ መስጠት መጀመራቸውን ተናግረዋል።
የአደጋ ጊዜ ፈጣን ምላሽ ሰጪ ማዕከላትና የህክምና ተቋማትን ማቋቋምና ማጠናከር ስራ እየተሰራ እንደሚገኝ አስረድተዋል፡፡
ሚኒስቴሩ ለጂንካ ሆስፒታል የማርበርግ ቫይረስን ለማከምና ለሌሎች ህክምናዎች የሚያስፈልጉ የተለያዩ የህክምና ቁሳቁሶችን ድጋፍ አድርጓል፡፡
ህብረተሰቡ ሚኒስቴሩ የሚያወጣቸውን መረጃዎች በመከታተል ራሱን እንዲጠብቅ አስገንዝበዋል።