ወ/ሮ ሜላተወርቅ ኃይሉ የብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ሰብሳቢ ሆነው ተሾሙ
አዲስ አበባ፣ ታኅሣስ 9፣ 2016 (ኤፍ ቢ ሲ) የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ዛሬ ባካሄደው 9ኛ መደበኛ ጉባዔ ወ/ሮ ሜላተወርቅ ኃይሉን የብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ሰብሳቢ አድርጎ ሾመ፡፡
በምክር ቤቱ የመንግሥት ተጠሪ ሚኒስትር ተስፋዬ ቤልጂጌ የወ/ሮ ሜላተወርቅ ኃይሉን የትምህርት ዝግጅት እና የሥራ ልምድ ለምክር ቤቱ ካቀረቡ በኋላ÷ በምክር ቤቱ አባላት ሐሳብና አስተያየት ተሰጥቶበታል፡፡
የምክር ቤቱ አባላት የሰጡትን ሐሳብና አስተያየት ተከትሎም ወ/ሮ ሜላተወርቅ ኃይሉ የብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ሰብሳቢ ሆነው እንዲሾሙ የቀረበለትን የውሳኔ ሐሳብ መርምሮ በአንድ ድምጸ ተዓቅቦ በአብላጫ ድምጽ አጽድቋል፡፡
ምክር ቤቱ የቀረበውን ሹመት የውሳኔ ቁጥር 2/2016 አድርጎ በአንድ ድምጸ ተዓቅቦ በአብላጫ ድምጽ አጽድቋል፡፡
ወ/ሮ ሜላተወርቅ ኃይሉም በምክር ቤቱ ቀርበው ቃለ መሐላ ፈጽመዋል፡፡
ወ/ሮ ሜላተወርቅ ኃይሉ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ የጽሕፈት ቤት ኃላፊ በመሆን ከየካቲት 2012 ዓ.ም እስከ የካቲት 2015 ዓ.ም አገልግለዋል።
ከዚህ ቀደም ቦርዱን በሰብሳቢነት ሲመሩ የነበሩት ብርቱካን ሚደቅሳ በጤና እክል ምክንያት ከነሐሴ 1 ቀን 2015 ዓ.ም ጀምሮ በገዛ ፈቃዳቸው ሥራቸውን መልቀቃቸው ይታወሳል፡፡
በዮሐንስ ደርበው