በማይናማር በአስቸጋሪ ሁኔታ ውስጥ የነበሩ 32 ኢትዮጵያዊያን ወደ ሀገራቸው ተመለሱ
አዲስ አበባ፣ መጋቢት 1፣ 2017 (ኤፍ ኤም ሲ) በማይናማር በእገታ እና በአስቸጋሪ ሁኔታ ውስጥ የነበሩ 32 ኢትዮጵያዊያን ወደ ሀገራቸው ተመልሰዋል፡፡
የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር እንዳስታወቀው÷ በህንድ ከሚገኘው የኢትዮጵያ ኤምባሲ ጋር በመተባበር ወደ ታይላንድ ከተሻገሩ 133 ኢትዮጵያዊያን መካከል 32ቱን ወደ ሀገራቸው መመለስ ተችሏል፡፡
43 ኢትዮጵያዊያን ዛሬ ምሽት ይገባሉ ተብሎ የሚጠበቅ ሲሆን÷ በታይላንድ ማቆያ የሚገኙ 58 ኢትዮጵያዊያንን ወደ ሀገራቸው ለመመለስ ኤምባሲው ጥረት እያደረገ ይገኛልም ተብሏል።
በተያያዘ መንግሥት ጃፓን በሚገኘው የኢትዮጵያ ኤምባሲ በኩል በማይናማር በአስቸጋሪ ሁኔታ ውስጥ የሚገኙ ሌሎች ኢትዮጵያዊያንን ወደ ታይላንድ በማሻገር ወደ ሀገራቸው ለመመለስ ጥረት እያደረገ እንደሚገኝ ተጠቁሟል፡፡
ሕብረተሰቡ በሕገ ወጥ የሰዎች አዘዋዋሪዎች ሀሰተኛ ቅስቀሳ ተታሎ የሥራ ስምሪት ውል ወዳልተፈጸመባቸው ሀገራት ከሚደረጉ እንቅስቃሴዎች እንዲቆጠብ ጥሪ መቅረቡን የሚኒስቴሩ መረጃ አመላክቷል፡፡