Fana: At a Speed of Life!

ዕለታዊ የአየር ሁኔታ ትንበያ ትክክለኛነት ወደ 80 በመቶ ከፍ ብሏል

አዲስ አበባ፣ ሐምሌ 16፣ 2017 (ኤፍ ኤም ሲ) የኢትዮጵያ ሚቲዎሮሎጂ ኢንስቲትዩት የዕለታዊ አየር ሁኔታ ትንበያ ትክክለኛነት 80 በመቶ ደርሷል አለ።

የኢንስቲትዩቱ ምክትል ዋና ዳይሬክተር አሳምነው ተሾመ (ዶ/ር) ከፋና ፖድካስት ጋር በነበራቸው ቆይታ እንዳሉት፤ የተቋሙ የአጭር፣ የመካከለኛና የረጅም ጊዜ የትንበያ ትክክለኛነት እየጨመረ መጥቷል።

የወቅቶች ወይም የረጅም ጊዜ ትንበያ ትክክለኛነቱ ወደ 78 በመቶ ያደገ ሲሆን የአጭር ጊዜ ወይም ዕለታዊ የትንበያ ትክክለኛነቱ ደግሞ ወደ 80 በመቶ ማደጉን አንስተዋል።

ተቋሙ ለትንበያ ስራው መረጃዎችን በሀገር ውስጥ ከሚገኙ የአየር ሁኔታ መረጃ መሰብሰቢያ ጣቢያዎችና ከዓለም አቀፍ ተቋማት እንደሚጠቀምም ገልጸዋል።

በሚቲዎሮሎጂ አከፋፈል ሶስት ወቅቶች እንዳሉ ገልጸው፤ ሀገራችን ከ85 በመቶ በላይ የሚሆነውን የዝናብ መጠን የምታገኘው በክረምት ወቅት ነው ያሉት።

ባለፈው ግንቦት ወር በክረምት ስለሚኖረው የዝናብ ስርጭት ለግብርና፣ ለውሃ፣ ለጤናና ለአካባቢ ጥበቃ የሚኖረውን ፋይዳ አስመልክቶ የትንበያ መረጃ መሰጠቱን አብራርተዋል።

ተቋሙ ወቅታዊና ፈጣን የአየር ሁኔታ መረጃዎችን ለህብረተሰቡ ከማድረስ አኳያ በክልሎች በሚገኙ 11 የሚቲዎሮሎጂ ማዕከላት ማህበረሰቡ በሚጠቀምበት ቋንቋ የትንበያና የቅድመ ማስጠንቀቂያ መረጃዎችን እያቀረበ መሆኑን አስረድተዋል።

በሚዲያ ተቋማት፣ በኢንስቲትዩቱ ማህበራዊ ሚዲያ አማራጮች ወቅታዊና ፈጣን መረጃዎችን ተደራሽ እያደረገ ነው ብለዋል።

በተለያዩ ጉዳዮች ዙሪያ ጥናት ለሚያደርጉ ዩኒቨርሲቲዎችና ግለሰቦች፣ ለአቪየሽን ዘርፍና በኢንቨስትመንት መሰማራት ለሚሹ ድርጅቶች በዘርፉ የሚያስፈልጋቸውን መረጃ ኢንስቲትዩቱ ያቀርባል ነው ያሉት።

ከ1 ሺህ 400 የሚቲዎሮሎጂ ጣቢያዎች እና ከ310 ዘመናዊ የአየር ሁኔታ መመዝገቢያ ጣቢያዎች የሚሰበሰብ መረጃ ወደ ማዕከል ገብቶ በሳይንሳዊ ቀመር ተተንትኖ የትንበያ፣ ቅድመ ማስጠንቀቂያና ምክረ ሃሳብ እንደሚሰጥም ጠቁመዋል።

በቴዎድሮስ ሳህለ

ፈጣን እና ወቅታዊ መረጃዎችን ለማግኘት፡-

YouTube www.youtube.com/@fanamediacorporation
Facebook www.facebook.com/fanabroadcasting
Telegram t.me/fanatelevision
Website www.fanamc.com
TikTok www.tiktok.com/@fana_television
WhatsApp www.whatsapp.com/channel/0029VbB0dRxG8l59MUkoWR29
Amharic Entertainment YouTube www.youtube.com/@fanaentertainment
Facebook www.facebook.com/wmccwaltamediaandcommunicationcorporate
TikTok www.tiktok.com/@fanamc_entertainment
Amharic Documentary YouTube www.youtube.com/@fanamcdocumentary በመወዳጀት ይከታተሉን፡፡
ዘወትር፦ ከእኛ ጋር ስለሆኑ እናመሰግናለን!

You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.