ጎንደር ዩኒቨርሲቲ በምርምር ሥራዎች የግብርና ዘርፉን ለማሳደግ እየሰራ ነው
አዲስ አበባ፣ ሐምሌ 26፣ 2017 (ኤፍ ኤም ሲ) ጎንደር ዩኒቨርሲቲ የተለያዩ የግብርና ምርምር ሥራዎችን በማከናወን ዘርፉን ለማሳደግ እየሰራ ነው አሉ የዩኒቨርሲቲው ፕሬዚዳንት አስራት አጸደወይን (ዶ/ር) ።
አስራት አጸደወይን (ዶ/ር) ጎንደር ዩኒቨርሲቲ የአርሶ አደሮችን ቀን ባከበረበት ወቅት እንዳሉት÷ ተቋሙ በግብርናው ዘርፍ ላደረጋቸው የምርምር ሥራዎች አርሶ አደሮች ከፍተኛ እገዛ አድርገዋል።
አርሶ አደሮች በዩኒቨርሲቲው ምስረታና ሒደት ከፍተኛ አበርክቶ እንደነበራቸው ጠቁመው ÷ ተቋሙ የአርሶ አደሮችን ውለታ መቼም አይዘነጋም ብለዋል።
ዩኒቨርሲቲው በግብርናው ዘርፍ ላይ የጀመራቸውን ጥረቶች በቀጣይ አጠናክሮ እንደሚቀጥልም አረጋግጠዋል።
የማዕከላዊ ጎንደር ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ አወቀ አስፈሬ በበኩላቸው÷በምግብ ራስን ለመቻል የሚደረገውን ጥረት ተቋማት በቴክኖሎጂ ማገዝ እንዳለባቸው አስገንዝበዋል፡፡
በመርሐ ግብሩ በግብርናው ዘርፍ ጎንደር ዩኒቨርሲቲ ባከናወናቸው ሥራዎች የላቀ አበርክቶ ለነበራቸው አርሶ አደሮችና ተቋማት እውቅና ተሰጥቷል፡፡
በምናለ አየነው