ኢትዮጵያ የጂኦግራፊ እስረኛ ሆና ለዘላለም ትኖራለች ብሎ የሚያስብ ኢትዮጵያዊ ካለ የሞተ ነው – ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ (ዶ/ር)
አዲስ አበባ፣ መስከረም 7፣ 2018 (ኤፍ ኤም ሲ) ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ኢትዮጵያ የጂኦግራፊ እስረኛ ሆና ለዘላለም ትኖራለች ብሎ የሚያስብ ኢትዮጵያዊ ካለ እርሱ የሞተ ነው አሉ።
ጠቅላይ ሚኒስትሩ በጻፉት “የመደመር መንግሥት” መጽሐፍ ምረቃ ሥነ ሥርዓት ላይ ባስተላለፉት መልዕክት÷ ኢትዮጵያ ሰላም አስቀድማ ድህነትን ትፋለማለች ብለዋል።
ኢትዮጵያ መውጫ መግቢያ በሯን ታበጃለች ይህ ጉዳይ የማይቀር ነው ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ÷ ይህ ሲሳካ ምናልባትም እኛ ላንኖር እንችላለን ነገር ግን ልጆቻችን በተዘጋ ሀገር ውስጥ የሚኖሩ ድሃ ሳይሆኑ የታሪክ ሰሪ ልጆች ሆነው ከራሳቸው አልፈው ሌሎች ሀገራትን የሚያግዙ ይሆናሉ ነው ያሉት።
ኢትዮጵያ የባህር በር ለማግኘት ጦርነት ያስፈልጋል ብላ እንደማታምን እንዲሁም ጥያቄዋን በሰላማዊ መንገድ ስታቀርብ እየደቆየች ገልጸው÷ ቀይ ባህርን መልሶ ለመጠየቅ የሚሰጋ እና የሚጠራጠር ትውልድ ሊኖር አይገባም ብለዋል።
ኢትዮጵያን ቆልፎ ድሃ ካደረጋት የባህር በር ችግር መገላገል አለባት ብለን እናምናለን፤ በዚህ ጉዳይ ላይ ከማንም ጋር በሰላማዊ መንገድ ለመምከር ፈቃደኞች ሲሉም አስገንዝበዋል።
ነገ ላይ ኢትዮጵያ ከራሷ አልፋ ወንድም ሀገራትን የምታግዝ መሆን አለባት፤ ይህ እውን እንዲሆን ደግሞ መንግስት ያስፈልጋል ያሉት ዐቢይ (ዶ/ር)÷ መንግስት ዛሬ ላይ ሆኖ ነገን ማወቅ አለበት ብለዋል።
በሶስና አለማየሁ
ፈጣን እና ወቅታዊ መረጃዎችን ለማግኘት፡-
Facebook www.facebook.com/fanabroadcasting
Telegram t.me/fanatelevision
Website www.fanamc.com
Amharic Entertainment YouTube www.youtube.com/@fanaentertainment
Amharic Podcast YouTube www.youtube.com/@fanamcpodcast በመወዳጀት ይከታተሉን፡፡
ዘወትር፦ ከእኛ ጋር ስለሆኑ እናመሰግናለን!