የኢነርጂ ፍላጎትን በዘላቂነት ለማሟላት የግል ዘርፉ ሚና
አዲስ አበባ፣ ጥቅምት 18፣ 2018 (ኤፍ ኤም ሲ) የውሃና ኢነርጂ ሚኒስቴር በኢትዮጵያ ያለውን የኢነርጂ ፍላጎት በዘላቂነት ለማሟላት የግል ዘርፉ ሚና የላቀ በመሆኑ ተሳትፎውን ማጠናከር ይገባል አለ።
ሁለተኛው የውሀና ኢነርጂ ሳምንት አውደ ርዕይ እና ፓናል ከትናንት ጀምሮ በሳይንስ ሙዚየም እየተካሄደ ይገኛል።
በዛሬው ዕለት በነበረ የፓናል ውይይት ላይ የውሃና ኢነርጂ ሚኒስትር ዴኤታ ሱልጣን ወሊ (ዶ/ር) እንዳሉት፤ ለሀገር ኢኮኖሚ እድገት ኢነርጂ ወሣኝነት አለው።
ቀጣይነት ያለው የኢነርጂ አቅርቦት ሀገራችን ለያዘችው ብልፅግና የጀርባ አጥንት ነው ብለዋል።
በኢትዮጵያ አብዛኛው ህብረተሠብ የማገዶ ተጠቃሚ በመሆኑ የእፅዋቶች መጠን እንዲቀንስ፣ የአየር ንብረት ለውጥ ጫና እንዲጨምር እና የአፈር መሸርሸር እንዲባባስ ማድረጉን ገልጸዋል።
ይህም የግብርና ምርታማነት ላይ አሉታዊ ተጽዕኖ በማስከተል የምግብ ዋስትና የማረጋገጥ ሂደትን ከማደናቀፍ ባለፈ በጭስ ምክንያት የበሽታ ተጋላጭነትን እንደሚጨምር ተናግረዋል።
ከለውጡ በኋላ የኢነርጂ አቅርቦት እየተሻሻለ መምጣቱን የገለጹት ሚኒስትር ዴኤታው፤ ፍላጎቱን ለማሟላት መስራት እንደሚያስፈልግ አመልክተዋል።
በመሆኑም የፖሊሲ ክለሳ በማድረግ የግል ዘርፉን ማሳተፍ ይገባል ማለታቸውን የሚኒስቴሩ የህዝብ ግንኙነት እና ኮሙኒኬሽን ስራ አስፈጻሚ ጌትነት ስሜ ለፋና ዲጂታል ገልጸዋል።