ሕብረተሰቡንና የተፈጥሮ ሀብቱን በማቀናጀት ለክልሉ ልማት እንሰራለን – አቶ ጥላሁን ከበደ
አዲስ አበባ፣ ነሐሴ 23፣ 2015 (ኤፍ ቢ ሲ) የክልሉን ሕብረተሰብና የተፈጥሮ ሀብት በማቀናጀት ለክልሉ ልማት እንሰራለን ሲሉ የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ጥላሁን ከበደ ተናገሩ።
አቶ ጥላሁን ከፋና ብሮድ ካስቲንግ ኮርፖሬት ጋር ባደረጉት ቆይታ÷ ክልሉ በገፀ ምድር እና በከርሰ ምድር ውሃ እንዲሁም በቡናና ፍራፍሬ ሀብት የታደለ መሆኑን ተናግረዋል።
የክልሉ መንግስትም ይህንን ፀጋ በመጠቀም በግብርናው ዘርፍ በምግብ እህል ራስን ከመቻል ባለፈ ለኢንዱስትሪው ግብአት ለማቅረብ ይሰራል ብለዋል።
ከቱሪዝም ዘርፍ የሚገኘውን ትሩፋት ለማሳደግም÷ ክልሉ የ10 ዓመት የልማት እቅድ ማዘጋጀቱን አንስተዋል።
የኦሞ ወንዝ ተፋሰስን በመጠቀም የክልሉን አርሶ አደሮች ተጠቃሚ የሚያደርጉ የመስኖ ልማቶችን ከማስፋፋት ባሻገርም የግል ባለሀብቱን በዘርፉ ለማሳተፍ የተለያዩ ሥራዎችም ይሰራሉ ነው ያሉት፡፡