ጠ/ሚ ዐቢይ (ዶ/ር) በፕሬዚዳንት ሺ ጂንፒንግ በተዘጋጀው የ’ቤልት ኤንድ ሮድ ፎረም’ የአቀባበል እራት ተደረገላቸው
አዲስ አበባ፣ ጥቅምት 6፣ 2016 (ኤፍ ቢ ሲ) ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) እና ቀዳማዊት እመቤት ዝናሽ ታያቸው በፕሬዚዳንት ሺ ጂንፒንግ በተዘጋጀው የ‘ቤልት ኤንድ ሮድ ፎረም‘ የአቀባበል እራት ላይ ተገኝተዋል።
የቻይናው ፕሬዚዳንት ሺ ጂንፒንግ በመርሐ ግብሩ ላይ አቀባበል እንዳደረጉላቸውም የጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት መረጃ ያመላክታል፡፡
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) እና የቻይናው ፕሬዚዳንት ሺ ጂንፒንግ ከየልዑካን ቡድናቸው ጋር በቻይና ታላቁ የሕዝብ አዳራሽ በሁለትዮሽ ጉዳዮች ላይ ተወያይተዋል፡፡
በውይይታቸውም÷ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ (ዶ/ር) የቻይና ኢንቨስትመንት ለኢትዮጵያ ኢኮኖሚ እመርታ የሚኖረውን አስተዋፅዖ አንስተዋል፡፡
በተለይም በአምስቱ ቁልፍ ምሰሶዎች ማለትም÷ በግብርና፣ ማኑፋክቸሪንግ፣ አይሲቲ፣ ማእድን ልማት እና ቱሪዝም ላይ ተጨማሪ ኢንቨስትመንት እንዲኖር የማበረታቻ ጥሪ አቅርበዋል፡፡