አንቶኒዮ ጉተሬዝ ለጋዛ እርዳታ የሚቀርብበትን የራፋህ መተላለፊያ ጎበኙ
አዲስ አበባ፣ ጥቅምት 9፣ 2016 (ኤፍ ቢ ሲ) የተባበሩት መንግስታት ድርጅት (ተመድ) ዋና ፀሐፊ አንቶኒዮ ጉተሬዝ በግብጽ ድንበር የሚገኘውንና ለጋዛ እርዳታ የሚቀርብበትን የራፋህ መተላለፊያን ጎብኝተዋል።
ጉተሬዝ እርዳታ ለማቅረብ የሚደረገውን ዝግጅት ተከትሎ በራፋህ ተገኝተው ጉብኝት ማድረጋቸው ተገልጿል።
የዕቃ ጫኝ አውሮፕላኖችና ከባድ ተሸከርካሪዎች ወደ ራፋህ ሰብዓዊ ዕርዳታ ለቀናት ሲያጓጉዙ ቢቆዩም እስካሁን ለጋዛ ሰርጥ ማድረስ እንዳልተቻለ ተገልጿል፡፡
ተሸከርካሪዎቹ በተቻለ ፍጥነት እርዳታውን ማድረስ እንዲችሉ ከሁሉም ወገኖች ማለትም ከግብፅ፣ እስራኤል እና አሜሪካ ጋር በአንክሮ እየመከሩ እንደሆነ ጉተሬዝ ለጋዜጠኞች መናገራቸውን ዘ ታይምስ ኦፍ ኢንዲያ ዘግቧል፡፡
ራፋህ በእስራኤል ቁጥጥር ሥር ያልገባ ወደ ፍልስጤም ድንበር መግቢያ ብቸኛው መተላለፊያ ሲሆን፤ እስራኤል በአሜሪካ ጥያቄ መሰረት በመስመሩ ሰብዓዊ እርዳታ እንዲያልፍ መስማማቷ ተገልጿል፡፡
የተባበሩት መንግስታት የሰብአዊ ድጋፍ ክፍል ሀላፊ ማርቲን ግሪፍስ የመጀመሪያው ድጋፍ ነገ ወይም ከነገ በኋላ በራፋህ በኩል እንደሚደርስ ጠቁመዋል፡፡
ወቅታዊ፣ትኩስ እና የተሟሉ መረጃዎችን ለማግኘት፡-
ድረ ገጽ፦ https://www.fanabc.com/
ቴሌግራም፦ https://t.me/fanatelevision
ትዊተር፦ https://twitter.com/fanatelevision በመወዳጀት ይከታተሉን፡፡
ዘወትር፦ ከእኛ ጋር ስላሉ እናመሰግናለን!