520 ሺህ ኩንታል ዩሪያ ማዳበሪያ የጫነች መርከብ ጅቡቲ ወደብ ደረሰች
አዲስ አበባ፣ ሕዳር 20፣ 2016 (ኤፍ ቢ ሲ) 520 ሺህ ኩንታል ዩሪያ የአፈር ማዳበሪያ የጫነች መርከብ ጅቡቲ ወደብ መድረሷን የኢትዮጵያ የግብርና ሥራዎች ኮርፖሬሽን አስታውቋል፡፡
ተጨማሪ 615 ሺህ ኩንታል ኤን ፒ ኤስ ቦሮን የጫነች መርከብም በነገው ዕለት ጅቡቲ ወደብ እንደምትደርስ ተገልጿል፡፡
በሌላ በኩል እስከ ታሕሳስ 3 ቀን 2016 ዓ.ም ድረስ ተጨማሪ 1 ሚሊየን 130 ሺህ ኩንታል ኤን ፒ ኤስ ቦሮን ጅቡቲ ወደብ እንደሚደርስ የኮርፖሬሽኑ መረጃ ያመላክታል፡፡
ለ2016/17 የምርት ዘመን ተገዝቶ ጅቡቲ ወደብ የደረሰውን የአፈር ማዳበሪያ ወደ ሀገር ውስጥ የማጓጓዝ ስራ እየተሰራ እንደሆነም ተጠቅሷል፡፡
ከዚህ ውስጥም 1 ሚሊየን 92 ሺህ 178 ኩንታል ዩሪያ ከጅቡቲ ወደብ ወደ ሀገር ውስጥ ተጓጉዞ ለአርሶ አደር ዩኒየኖች እየተሰራጨ ነው ተብሏል፡፡