ኢትዮጵያና ካዛኪስታን በተለያዩ ዘርፎች ያላቸውን ግንኙነት ለማጠናከር ተወያዩ
አዲስ አበባ፣ ታኅሣስ 20፣ 2016 (ኤፍ ቢ ሲ) የኢትዮ- ካዛኪስታን የፓርላማ ዲፕሎማሲ ወዳጅነት ቡድን ከካዛኪስታን አቻው ጋር የሁለትዮሽ ውይይት በበይነ መረብ አካሄዷል።
በውይይታቸውም የሁለቱን ሀገራት ትብብር እና የፓርላማ ግንኙነት ማጠናከር በሚቻልባቸው ጉዳዮች ላይ መክረዋል፡፡
የኢትዮ-ካዛኪስታን ወዳጅነት ቡድን ሰብሳቢ ቤተልሄም ላቀው (ዶ/ር)÷ መሰል ውይይት መጀመሩ ሀገራቱን ይበልጥ የሚያቀራርብ መሆኑን አንስተዋል።
ሁለቱ ሀገራት በማደግ ላይ ያሉ እና በርካታ የሚያመሳስላቸው ነገሮች ያሉ መሆኑን ገልፀው÷ ሁለቱም የባህር በር የሌላቸው በመሆኑ በእነዚህና መሠል ዘርፎች በጋራ መስራት አንደሚገባቸው ጠቁመዋል፡፡
የካዛኪስታን ወዳጅነት ቡድን ሰብሳቢ ዛሃረኬነብክ አማንቲውሊ በበኩላቸው÷ ሁለቱ ሀገራት በግብርና፣ በትምህርትና በሌሎችም ዘርፎች አብረው መስራት እንደሚችሉ ተናግረዋል፡፡
በፓርላማ ዲፕሎማሲ፣ በቴክኖሎጂ፣ በንግድ እና በሌሎችም ዘርፎች ያላቸውን ግንኙነት ማጠናከር እንደሚገባ መግለጻቸውንም የም/ቤቱ መረጃ ያመላክታል፡፡
ውይይቱ የሀገራቱን ግንኙነት ለማጠናከር፣ ከፓርላማ አባላት የሚጠበቀውን ሚና ለማመላከት፣ የግንኙነት መስኮችንና የወደፊት የትብብር እድሎችን መጠቀም በሚያስችሉ ጉዳዮች ላይ ያተኮረ መሆኑ ተጠቅሷል፡፡