የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ የሰብል ምርት ብክነትን ማስወገድ ይገባል – ግርማ አመንቴ (ዶ/ር)
አዲስ አበባ፣ ሐምሌ 29፣ 2016 (ኤፍ ቢ ሲ) የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ የሰብል ምርት ብክነትን ማስወገድ ይገባል ሲሉ የግብርና ሚኒስትሩ ግርማ አመንቴ (ዶ/ር) ተናገሩ፡፡
የተመጣጠነ የአመጋገብ ስርዓት ያለው ማህበረሰብ ጤናን ከመጠበቅ ባለፈ በተሰማሩበት የስራ መስክ ሁሉ በተሻለ መልኩ ውጤታማ ይሆናሉ ብለዋል፡፡
የምግብ ዋስትናን ማረጋገጥ የግብርናውን ዘርፍ ምርታማነትን ከመጨመር ባለፈ በቤተሰብ የስርዓተ–ምግብ ሁኔታ ላይ ከፍተኛ ሚና እንደሚኖረውም ተናግረዋል፡፡
እንደ ሀገር በድህረ–ምርት አያያዝ ወቅት በፍራፍሬ ምርት 50 በመቶ እንዲሁም በሰብል ምርት 30 በመቶ ምርት እንደሚባክን ገልፀው÷ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ የምርት እና የፍራፍሬ ምርቶችን ብክነት መቀነስ እንደሚገባ ጠቅሰዋል፡፡
ግብርና እና ስርዓተ–ምግብ የጠበቀ ግንኙነት አላቸው ያሉት ሚኒስትሩ÷ የምግብና ሥርዓተ–ምግብ ጉዳይ የብዙ ባለድርሻ አካላትን ትብብርና ቅንጅት የሚጠይቅ ሰፊ ሥራ መሆኑን አስገንዘበዋል፡፡
ይሁን እንጂ ከዚህ ከበፊት በነበረው ውጤታማ ያልሆነ የግብርናው ዘርፍ ፖሊሲና ስትራቴጂ ተግባራዊ በመደረጉ ምክንያት የምግብ እና ስርዓተ ምግብ ጉዳይ ትኩረት ሳይሰጠው መቆየቱን ማንሳታቸውን የግብርና ሚኒስቴር መረጃ አመላክቷል።
አሁን ላይ የተሻሻለ የግብርና ፖሊሲ ተግባራዊ መደረጉን ገልጸው÷ በዚህም በግብርናው ዘርፍ ውስጥ የሚተገበሩ ፕሮግራሞች፣ ፕሮጀክቶች እንዲሁም ስትራቴጂዎች ስርዓተ–ምግብ ተኮር እንዲሆኑ ምቹ ሁኔታዎችን ይፈጥራሉ ብለዋል፡፡