Fana: At a Speed of Life!

አዲሱ የተሽከርካሪዎች ሰሌዳ ሀገርን የሚመጥን የፖሊስ አገልግሎት መስጠት ያስችላል – ኮሚሽነር ጀነራል ደመላሽ ገ/ሚካኤል

አዲስ አበባ፣ ጥር 28፣ 2018 (ኤፍ ኤም ሲ) የኢትዮጵያ ፌዴራል ፖሊስ ኮሚሽነር ጀነራል ደመላሽ ገ/ሚካኤል አዲሱ የኢትዮጵያ ፌደራል ፖሊስ የተሽከርካሪ ሰሌዳ ሀገርን የሚመጥን የፖሊስ አገልግሎት መስጠት ያስችላል አሉ።

ኮሚሽነር ጀነራል ደመላሽ ገ/ሚካኤል የተሽከርካሪ ሰሌዳ ለውጥ መደረጉ ሕገ ወጥ ድርጊቶችን በመከላከል እና በመቆጣጠር የዜጎችን ደህንነት ለማረጋገጥ እንደሚያግዝ አስረድተዋል፡፡

ነባሩ የፌዴራል ፖሊስ ተሽከርካሪ ሰሌዳ ከ50 ዓመታት በላይ የቆየ፣ የተዘበራረቀና ወጥነት የጎደለው እንደነበር አስታውሰው÷ ይህም ለቁጥጥር አመቺ እንዳይሆን ማድረጉን አብራርተዋል፡፡

ፖሊስ ሀገርና ዘመኑን የሚመጥን አገልግሎት ለመስጠት በትኩረት እየተሰራ ይገኛል ያሉት ኮሚሽነር ጀነራሉ ÷ አዲሱ የፖሊስ ሰሌዳ በስራ ላይ መዋሉ የወንጀል ምርመራና ክትትል ስራን ማዘመንና ማሳለጥ እንደሚያስችል አጽንኦት ሰጥተዋል፡፡

አዲሱ የተሽከርካሪዎች ሰሌዳ ከቴክኖሎጂ እና ከመረጃ ቋት ጋር የተጣመረ መሆኑን ገልጸው÷ መሰል አገልግሎቶችን ከቴክኖሎጂ ጋር የማስተሳሰር ስራዎች የዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ጉዞ ማሳያ እንደሆኑ ጠቅሰዋል።

የትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ ሚኒስትር ዴዔታ በርኦ ሀሰን በበኩላቸው ÷ የኢትዮጵያ ፌዴራል ፖሊስ የተሽከርካሪ ሰሌዳ ለውጥ ዘመኑን የዋጀና ኢትዮጵያ ለቴክኖሎጂ የሰጠችውን ትኩረት የሚያሳይ ነው ብለዋል፡፡

እንደ ሀገር አጠቃላይ የተሽከርካሪ ሰሌዳ ለውጥ ሥራን ለማጠናቀቅ በትኩረት እየተሰራ እንደሚገኝም ነው ያመላከቱት፡፡

በጀማል አህመድ

You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.