የፋና ላምሮት ምዕራፍ 22 ውድድር በመጪው ቅዳሜ ይጀመራል
አዲስ አበባ፣ መጋቢት 1፣ 2018 (ኤፍ ኤም ሲ) ከ700 በላይ የቅድመ ማጣሪያ ተፎካካሪዎች መካከል የተለዩ 16 ከዋክብትን በመያዝ የፋና ላምሮት ምዕራፍ 22 ውድድር በመጪው ቅዳሜ መካሄድ ይጀምራል።
በምዕራፉ የመጀመሪያ ሳምንት ውድድር ስምንት ተወዳዳሪዎች ከዛየን ባንድ ጋር ስራዎቻቸውን በሁለት ዙር ያቀርባሉ።
ለ13 ሳምንታት በሚዘልቀው በዚህ ምዕራፍ ተወዳዳሪዎች በተለያዩ ሳምንታት በራሳቸው፣ በዳኞች እና በተመልካቾች የሙዚቃ ምርጫ ብርቱ ፉክክር ያደርጋሉ።
የሙዚቃ ባለሙያዎች እና ተመልካቾች ባልተገደበ አጭር የጽሑፍ መልዕክት በሚሰጡት ድምጽ ተወዳዳሪዎቹ የሚዳኙ ይሆናል።
በምዕራፉ ለፍፃሜ ለሚደርሱ አራት ተወዳዳሪዎች የ1 ሚሊየን ብር ሽልማት የተዘጋጀ ሲሆን፤ ለፋና ላምሮት 6ኛው የአሸናፊዎች አሸናፊ ውድድር በቀጥታ ያልፋሉ።
የምዕራፍ 22 ውድድር በመጪው ቅዳሜ መጋቢት 5 ቀን 2018 ዓ.ም ከቀኑ ከ6:00 ጀምሮ በቀጥታ ስርጭት ይተላለፋል።
በመሆኑም ውድድሩን በፋና ቴሌቪዥን፣ በፋና+፣ በፋና ፌስቡክ፣ በፋና ዩቲዩብ እና ቴሌግራም ገጾች እንዲሁም በ www.fanamc.com ይከታተሉ።
ፋና ላምሮት ከ2011 ዓ.ም መጨረሻ ጀምሮ የበርካታ ባለተሰጥኦ ድምፃውያን መፍለቂያ በመሆን ለኪነ ጥበብ ዕድገት አሻራውን እያኖረ ይገኛል።