Fana: At a Speed of Life!

ሰላማዊ መንገድ እንዳይዘጋ፣ ዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ ህወሓትን ወደ ሰላም መንገድ እንዲያመጣው መንግስት አሳሰበ

አዲስ አበባ፣ ነሐሴ 20፣ 2014 (ኤፍ ቢ ሲ) ሰላማዊ መንገድ እንዳይዘጋ፣ ዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ ህወሓትን ወደ ሰላም መንገድ እንዲያመጣው መንግስት አሳሰበ።
የመንግሥት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት በወቅታዊ ጉዳይ ላይ ጋዜጣዊ መግለጫ አውጥቷል።
ያለ ጦርነት መኖር የማይችለው ህወሓት ለሰላም የተከፈቱትን በሮች ሁሉ እየዘጋቸው ነው ያለው መግለጫው፥ የመከላከያ ኃይላችን ይዞ በቆየባቸው ቦታዎች ላይ አሁንም ጥቃት እየፈጸመ መሆኑን አስታውቋል፡፡
የመከላከያ ኃይል የመንግሥትን የሰላም አማራጭ በመያዝ በጥንቃቄ በመከላከል ላይ መሆኑንም ነው ያመለከተው።

የኢትዮጵያ መንግሥት ለሰላም ያደረገው ጥረትና የከፈለው ዋጋ መኖሩን የጠቀሰው መግለጫው፥ መንግሥት በሰሜኑ የሀገሪቱ ክፍል የተፈጠረውን ችግር በሰላማዊ መንገድ ለመፍታት ውሳኔ ማሳለፉን ገልጿል፡፡

በውሳኔው መሠረት የተናጠል ተኩስ አቁም ማድረጉን፣ ለእርዳታ የሚገቡ ተሽከርካሪዎች እና ቁሳቁሶች ላልተገባ ተግባር መዋላቸውን እያወቀ እንኳን÷ ለሕዝብ ሲባል ወደ ትግራይ ክልል ሰብዓዊ እርዳታ እንዲገባ ሁኔታዎችን አመቻችቷል ነው ያለው፡፡

የድርድር ዕቅዱን እና ተደራዳሪዎቹን ይፋ በማድረግ፥ በየትኛውም ጊዜ፣ ቦታ እና ጉዳይ ለመነጋገር ዝግጁ መሆኑንም መንግሥት አስታውቋል፡፡

ዓለም አቀፉ ማህበረሰብ አሁን በግልጽ እንደታየው ህወሓት ነዳጅ ዘራፊ ብቻ ሳይሆን ጠብ ጫሪ መሆኑንም አውቆ ማውገዝ እንዳለበት ነው የገለፀው፡፡

ዓለም አቀፉ ማህበረሰብ “ሁለቱ ወገኖች” ከሚል ፍርደ ገምድል ጥሪ ተላቆ መንግሥት ወደያዘው የሰላም አማራጭ ህወሓት እንዲመጣ ግፊት እንዲያደርግ መንግሥት ጥሪ አቅርቧል፡፡

ይህ ካልሆነ እና ህወሓት ጥቃቱን የሚቀጥል ከሆነ መንግሥት በሕግ የተጣለበትን ግዴታ ለመወጣት ሲል ማንኛውንም እርምጃ ለመውሰድ የሚገደድ መሆኑን አስታውቋል፡፡

You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.