ከ510 ሚሊየን ብር በሚልቅ ወጪ የቃሊቲ ወደብና ተርሚናል ግንባታ ሊከናወን ነው
አዲስ አበባ፣ የካቲት 27፣ 2017 (ኤፍ ኤም ሲ) ከ510 ሚሊየን ብር በሚልቅ ወጪ የቃሊቲ ወደብና ተርሚናል ግንባታን ለማከናወን የሚያስችል ስምምመት ተፈረመ፡፡
የኢትዮጵያ የባሕር ትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ የቃሊቲ ወደብና ተርሚናል ደረጃውን በጠበቀ መልኩ ለማስገንባት የሚያስችከለውን ስምነት ከኢትዮጵያ ኢንጂነሪንግ ኮርፖሬሽን ጋር ተፈራርሟል፡፡
በዚሁ ወቅት የቃሊቲ ወደብና ተርሚናል ለሠራተኞችም ሆነ ለአገልግሎት ተጠቃሚ ደንበኞች ምቹ አለመሆኑን የኢትዮጵያ የባሕር ትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ ዋና ሥራ አስፈፃሚ በሪሶ አመሎ (ዶ/ር) ገልጸዋል፡፡
በመሆኑም በስምምነቱ መሠረት ፕሮጀክቱ በወቅቱ እንዲጠናቀቅ በማድረግ በአጭር ጊዜ ውስጥ ምቹ የሥራ አካባቢን እንፈጥራለን ብለዋል፡፡
የኢትዮጵያ ኢንጂነሪንግ ኮርፖሬሽን ዋና ሥራ አስፈፃሚ ሽመልስ እሸቱ (ኢ/ር) በበኩላቸው፤ ግንባታውን ከተቀመጠለት ጊዜ ባጠረና በከፍተኛ ጥራት ለማጠናቀቅ እንደሚሠሩ አረጋግጠዋል፡፡
አጠቃላይ ሥራው በሥድስት ወራት እንደሚጠናቀቅ በስምምነቱ ላይ ተገልጿል፡፡