በትግራይ ክልል የበረሃ አንበጣን ለመከላከል ከ10 ሚሊየን ብር በላይ ለመለገስ ቃል ተገባ
አዲስ አበባ፣ ጥቅምት 13፣ 2013 (ኤፍ.ቢ.ሲ) በትግራይ ክልል የበረሃ አንበጣን ለመከላከል በተደረገ የገቢ ማሰባሰቢያ መርሃ ግብር ከ10 ሚሊየን ብር በላይ ቃል ተገባ።
በክልሉ የበረሃ አንበጣን ለመከላከል የተቋቋመው ጊዜያዊ የድጋፍ አሰባሳቢ ኮሚቴ ትናንት ምሽት በሸራተን አዲስ ሆቴል የገቢ ማሰባሰቢያ መርሃ ግብር አካሂዷል።
መርሃ ግብሩ በትግራይ ተወላጅ ባለሀብቶችና በትግራይ ብልጽግና ፓርቲ አመራሮች አስተባባሪነት ነበር የተካሄደው።
በመርሃ ግብሩ በክልሉ የበረሃ አንበጣን ለመከላከልና የአንበጣ መንጋ ባደረሰው ጉዳት ለተጎዱ ወገኖች ባለሀብቶችና ድርጅቶች ድጋፍ ለማድረግ ቃል ገብተዋል።
ችግሩን ለማቃለል ድጋፍ እየተሰባሰበ መሆኑን አስተባባሪዎቹ ገልጸዋል።
የኮሚቴው የበላይ ጠባቂ የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር ዶክተር አብርሃም በላይ፤ መርሃ ግብሩ በትግራይ ክልል የተከሰተውን የበረሃ አንበጣ መንጋ ለማጥፋት ለኬሚካል ግዢና ጉዳት የደረሰባቸውን አርሶ አደሮች ለመደገፍ መዘጋጀቱን ተናግረዋል።
በርካታ ባለሀብቶች የሚያደርጉትን ድጋፍ እንዲያጠናክሩ ሚኒስትሩ ጠይቀዋል።
መርሃ ግብሩ “ትግራይ ትጣራለች”፣ “የአብሮነትና የድል ታሪካችን አንበጣ ላይ ይደገማል”፣ “የገበሬው ህልውና የሀገር ህልውና ነው” በሚሉ መሪ ቃሎች መካሄዱን ኢዜአ ዘግቧል፡፡
በኢትዮጵያ ንግድ ባንክ 1000349168166 እና በወጋገን ባንክ 0848379030101 ድጋፍ ማድረግ እንደሚቻልም ተገልጿል።